አዲስ አበባ, መጋቢት 5 ቀን 2002 (አዲስ አበባ) - በኮልፌ ቀራኒዮ ክፍለ ከተማ 30 ሚሊዮን ብር በሚጠጋ ወጪ የተገነቡ የልማት ሥራዎች ዛሬ ተመረቁ፡፡የአዲስ አበባ ከተማ ከንቲባ አቶ ኩማ ደመቅሳ ኅብረተሰቡ የሚጠበቅበትን ግብር አጠናቅቆ መክፈል ከቻለ የከተማው አስተዳደር የሚያከናውናቸውን የልማት ሥራዎች በይበልጥ ማስፋፋት እንደሚቻል ገልጸዋል፡፡
የኮልፌ ቀራኒዮ ክፍለ ከተማ ሥራና ከተማ ልማት ጽህፈት ቤት ኃላፊ አቶ ገዛኸኝ ኃይሌ የልማት ሥራዎቹ ሲመረቁ እንዳስታወቁት የክፍለ ከተማው አስተዳደር በራሱ ወጪ ያከናወናቸው የልማት ሥራዎች 21 ነጥብ 2 ሚሊዮን ብር ያህል ወጪ አድርጓል፡፡
ከልማት ሥራዎቹ መካከል የሁለት ባለ አራት ፎቅ ትምህርት ቤቶች ማስፋፊያ ሕንፃዎች ግንባታ ፣አምስት የስፖርት ማዘውተሪያ ሜዳዎች፣ ሁለት ባለ ሦስት ፎቅ የወጣት ማዕከል ይገኙባቸዋል፡፡
አንድ ዘመናዊ ባለ አራት ፎቅ የሽመና ማዕከልና አንድ ጤና ጣቢያ መገንባታቸውንም ኃላፊው አስታውቀዋል፡፡
የስድስት ቀበሌዎች ሕዝብ በማስተባበር ደግሞ ከስምንት ነጥብ አንድ ሚሊዮን ብር በሚበልጥ ወጪ የአስፋልትና የገረጋንቲ መንገዶች ፣የእግረኛ መሸጋገሪያ ድልድይ ድጋፍና የውሃ ማስወገጃ ተሰርተዋል፡፡
ምረቃ ከተደረገላቸው ሌላ የስምንት ባለአራት ፎቅ የጤና ጣቢያዎች፣ የሰባት ባለ አራት ፎቅ ትምህርት ቤት ግንባታዎች እንዲሁም የአራት ባለሦስት ፎቅ የወጣት ማዕከሎችና ሌሎች የልማት ሥራዎች ግንባታ በመፋጠን ላይ እንደሚገኝ አቶ ገዛኸኝ ገልጸዋል፡፡
የአዲስ አበባ ከተማ ከንቲባ አቶ ኩማ ደመቅሳ በምረቃው ላይ ባሰሙት ንግግር የከተማዋ አስተዳደር ከ2001 ጀምሮ የከተማዋን ዘርፈ ብዙ ችግሮች ደረጃ በደረጃ ለመፍታት ከፍተኛ እንቅስቃሴ እያደረገ ነው ብለዋል፡፡
አስተዳደሩ በአጭር፣ በመካከለኛና በረጅም ጊዜ ለማሰራር ያቀዳቸው የልማት ሥራዎች ለማሳካት የከተማዋ ነዋሪዎች ድጋፍ ማድረግ ይጠበቅባቸዋል።
በመሆኑም የከተማዋ ነዋሪዎች የሚፈለግባቸውን ግብር በመክፈል ከተማዋን ለማልማት የሚካሄደውን ጥረት እንዲያግዙ አሳስበዋል፡፡
ስ 4፡00 ሪ 8፡00 ያ 9፡15 ተ 9፡35 ጠሰድ 5፡35 ጥከ
---END---