በአዲስ አበባ ከተማ በመገንባት ላይ ያለው የኦሮሞ ባህል ማዕከል ግንባታ 40 በመቶ ተጠናቀቀ
አዲስ አበባ, መጋቢት 4 ቀን 2002 (አዲስ አበባ) -

በኦሮሚያ ብሔራዊ ክልላዊ መንግስት ወጪ በ168 ነጥብ 74 ሚሊዮን ብር በአዲስ አበባ ቂርቆስ ክፍለ ከተማ የሚገነባው የኦሮሚያ ባህል ማዕከል ግንባታ በመጠናቀቅ ላይ እንደሚገኝ ተገለጸ።

በ4 ነጥብ 1 ሄክታር ላይ የሚገነባውን የባህል ማዕከል በየካ ክፍለ ከተማ የሚኖሩ የብሔሩ ተወላጆች ዛሬ ተዘዋውረው ጎብኝተዋል።

የባህል ማዕከሉ ዘጠኝ ሕንፃዎች በ2 ነጥብ 7 ሄክታር ላይ የሚገነቡ ሲሆን ግንባታቸው ጥቅምት 26 ቀን 2001 ዓ.ም. የተጀመረ ሲሆን በአሁኑ ወቅት 40 በመቶው ተጠናቋል።

የክፍለ ከተማው የኢትዮጵያ ሕዝቦች አብዮታዊ ዴሞክራሲያዊ ግንባር /ኢህአዴግ/ ጽህፈት ቤት የሕዝብ ግንኙነት አማካሪ አቶ ደረጀ አበራ የጉብኝቱን ዓላማ በተመለከተ እንደተናገሩት በኦሮሚያ ብሔራዊ ክልላዊ መንግስት እየተከናወኑ ያሉ የልማት ሥራዎችን ለብሔሩ ተወላጆች ግንዛቤ ለማስጨበጥ ነው።

በክልሉ እየተካሄደ ያለው ልማት እንዲፋጠን የብሔሩ ተወላጆች በቀበሌ ደረጃ በማህበር ተደራጅተው እየተንቀሳቀሱ እንደሚገኙም ገልጸዋል።

የባህል ማዕከሉ መገንባት የኦሮሞ ሕዝብ ባህልና ቋንቋ ተጠብቆ እንዲቆይ ከፍተኛ አስተዋጽኦ እንዳለው ተናግረዋል።

መንግስት ድህነትን ለመቀነስ በሚያደርገው ርብርብ የክልሉ ተወላጆች በልማቱ ተሳታፊ በመሆን የበኩላቸውን ድርሻ እንዲወጡ አሳስበዋል።

የክልሉ ተወላጆች በጉብኝቱ ወቅት እንዳሉት ኢትዮጵያን በአጭር ጊዜ መካከለኛ ገቢ ካላቸው አገሮች ተርታ ለማሰለፍ በሚደረገው ርብርብ መንግስት ጎን በመቆም የበኩላቸውን ድርሻ እንደሚወጡ ገልጸዋል።

በጉብኝቱ የኦሮሚያ ብሔራዊ ክልላዊ መንግስት ከፍተኛ የሥራ ኃላፊዎች ተገኝተዋል።

የባህል ማዕከሉ ሙዚየም፣ ቲያትር ቤት፣ ቤተ መጽሐፍት፣ የቋንቋ አካዳሚና ወመዘክር፣ የስብሰባ አዳራሽና ሬስቶራንት አካቷል። እንዲሁም እስከ 400 ተሽከርካሪዎች የሚያስተናግድ የመኪና ማቆሚያ ስፍራ አለው። ግንባታው በ14 ወራት ውስጥ ይጠናቀቃል ተብሎ ይጠበቃል።

---END---

Headlines
የተቃዋሚ የፖለቲካ ፓርቲዎች እጩዎችና ተወካዮች የመራጮችና እጩዎች ምዝግባ ሂደት ዴሞክራሲያዊ መሆኑን ገለጹ
በአዲስ አበባ ከተማ በመገንባት ላይ ያለው የኦሮሞ ባህል ማዕከል ግንባታ 40 በመቶ ተጠናቀቀ
በአዶላ ሬዴ ወረዳ እንስሳት ያደለቡ 29 ሚሊዮን ብር ገቢ አገኙ
በሐውዜን ወረዳ የተለያዩ የልማት ስራዎች እየተከናወኑ ነው
በወላይታ የሚገኙ የመስህብ ስፍራዎችን ከ40 ሺህ በላይ ቱሪሰቶች ጎበኙ
በደቡብ ክልል ከ174 ሺህ በላይ ግብር ከፋዬችን የጣት አሻራ ተመዝግበዋል
(c) The Ethiopian News Agency