አዲስ አበባ, ጥር 2 ቀን 2000 (አዲስ አበባ) - በሒጂራ አቆጣጠር የዘመን መለወጫ በገባ በ10ኛው ቀን የሚከበረው አንድ ሺህ 429ኛዉ አመት የአሹራ በዓል ጥር 9 ቀን 2000 ዓ.ም በትግራይ በነጃሺ ከተማ በድምቀት ይከበራል፡፡ በየዓመቱ በነጃሺ ከተማ ይከበር የነበረው ይህ በዓል በአገር አቀፍ ደረጃ ሲከበር የዘንድሮው ለመጀመሪያ ጊዜ ይሆናል፡፡
በዓሉ እስልምና ወደኢትዮጵያ ከገባበት ጊዜ ጀምሮ የመጀመሪያዎቹ ሙስሊሞች በሰፈሩበት ነጃሺ ከተማ ያሉትን የታሪክ አሻራዎች ለዓለም ለማስተዋወቅ እንደሚረዳ የኢትዮጵያ እስልምና ጉዳዮች ጠቅላይ ምክር ቤት ምክትል ፕሬዚዳንት ሼክ ኤልያስ ሬድማን ዛሬ ለኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት ገልፀዋል፡፡
የነጃሺ ከተማ ተቻችሎ መኖርን ለዓለም የሚሰብክ ታሪክ የያዘ ቦታ መሆኑን የገለጹት ሼክ ኤልያስ ቦታው የኢትዮጵያ ብቻ ሣይሆን የአፍሪካ ብሎም የዓለም ሀብት ነው ብለዋል፡፡፡
የነጃሺ ከተማና መስጊድ በኤርትራ እንደሚገኝ በማስመሰል ከኤርትራ የሚሰጡት መግለጫዎች ሀሰት መሆኑን ለዓለም ለማሳየትና በዓሉን ከትክክለኛ ቦታው ለመዘገብ ከሱዳን የናይል ቴሌቪዥን ጋዜጠኞችም እንደሚመጡም ገልፀዋል፡፡
በበዓሉ ላይ ዲፕሎማቶች፣ ከተለያዩ የአገሪቱ ክፍል እንዲሁም ከውጪ የሚመጡ እንግዶች ይገኛሉ፡፡ ለበዓሉ የሚመጡትን እንግዶች በአግባቡ ለማስተናገድ አስፈላጊው ዝግጅት መጠናቀቁን ገልፀዋል፡፡
በዓሉ በእምነቱ ትልቅ ስፍራ የሚሰጠውን የነጃሺ ከተማ ለዓለም ከማስተዋወቁም በላይ ከተማዋን የቱሪስት መዳረሻ ለማድረግና በዓለም ቅርስነት ለማስመዝገብ የሚደረገውን ጥረት እንደሚያግዝ ተገልጿል፡፡
የነጃሺና የነብዩ መሀመድ ተከታዮች መቃብር እንዲሁም ጥንታዊውን የነጃሺ መስጊድ የያዘችውን የነጃሺ ከተማ ድንበር የሚለይና የቱሪስት መዳረሻ ለመሆን የሚያስችላትን ሥራዎች ቅድመ ሁኔታዎች እየተጠናቀቁ ነው፡፡
ይህንን ታሪካዊ በዓል ሁሉም ኢትዮጵያውያን በአንድነት እንዲያከብሩ ጠይቀዋል፡፡
ስ-3፡00 መ-6፡07 ሪ-6፡10 ያ-6፡30 ኤያ/6፣45ጥከ
---END---