አዲስ አበባ, ጳጉሜን 1 ቀን 1999 (አዲስ አበባ) - ኢትዮጵያ ውስጥ ለተጓዦችና ለአገር ጎብኝዎች አቅጣጫዎችን በመጠቆም የመረጃ አገልገሎት የሚሰጥ ''ግሎባል ፖዚሽ ሶሉሽን'' /ጂፒኤስ/ የተባለ አዲስ ቴክኖሎጂ ተግባራዊ ሊሆን ነው፡፡ 27 ሺህ መንደሮችን፣ ከተሞችንና ወረዳዎችንና ያካተተ መሆኑን የፈጠራው ባለቤት ገለጹ፡፡ይህንኑ ቴክኖሎጂ በሸራተን አዲስ በተግባር ሲሞከር የቱሪዝምና የባህል ሚኒስተሩ አምባሳደር ሙሐመድ ዲሪር እንደገለጹት የዚህ አይነቱ ዘመናዊ የመረጃ ቴክኖሎጂ ኢትዮጵያ ውስጥ ተግባራዊ መሆኑለቱሪስቶች ጠቃሚ ነው ፡፡
የመረጃ መሳሪያው በተለይ ለተጓዦችና ለቱሪስቶች ወደሚፈልጉበት ለመሄድና አግልግሎት ለማግኘት ለሚያደርጉት ጥረት ጠቀሜታው ከፍተኛ መሆኑን አምባሳደር መሐመድ ጠቁመዋል፡፡
በኢትዮጵያ ብዛት ያላቸው የቱሪስት መስህቦች በተለያዩ ከተሞችና አካባቢዎች ቢገኙም ሃብቶቹ የሚገኙበትን ትክክለኛ ስፍራ በካርታም ሆነ በሌላ መረጃ ለተጓዦች አቅጣጫ የሚያመለክት በቂ መረጃ አለመኖሩን ተናገረዋል፡፡
በተለያዩ የዓለም ክፍሎች የጂፒኤስ አቅጣጫ ጠቋሚ መሳሪያ ከቱሪስት መስህቦች በተጨማሪ የአገልገሎት መስጫ ተቋማትን አድራሻና አቅጣጫ በማመላከት ረገድ አግር ጎብኚዎች እንዳይቸገሩ እንደሚያደርግም አስታውቀዋል፡፡
የፈጠራው ባለቤት አቶ አካሉ ዓለሙ እንደጠቆሙት ቴክኖሎጂው ኢትዮጵያ ውስጥ አዲስና ለመጀመሪያ ጊዜ ተግባር ላይ የዋለ ነው፡፡
መሳሪያው በሳተላይት የሚታገዝና ኢትዮጵያውስጥ የሚገኙ 27 ሺህ መንደሮች ፣ወረዳዎችንና ከተሞችን በጉዞ ወቅት የሚያመላክት መሆኑን ገለጸው አንድ አገልግሎት ፈላጊ ተጓዥ ካለበት ቦታ ሆኖ በቅርብ ርቀት ካለው ከተማ ምንአይነት አገልግሎት ማግኘት እንደሚችል በቀላሉ ማወቅይቻለዋል ብለዋል፡፡
የኢትዮጵያን ተፈጥሯዊና ታሪካዊ ሥፍራዎችን ጨምሮ የትራንሰፖርት ድርጅቶች፣የነዳጅ ማደያዎች ፣የሆቴሎች፣ የሬስቶራንቶች፣የባንክቤቶች እና ሌሎች ጠቃሚ መረጃዎችን መሳሪያው የሚያቀርብ መሆኑንና ወደፊትም እየተሻሻለ እንደሚሄድ ተናግረዋል፡፡፡
---END---