አዲስ አበባ, ጥቅምት 15 ቀን 2000 (አዲስ አበባ) - በቅርቡ ኤች አር 2003 የሚባል መጠሪያ የተሰጠውና ከኢትዮጵያ ብሔራዊ ጥቅም በተፃራሪ በቆሙ ኃይሎች ግፊት በአሜሪካ መንግስት ሴኔት እንዲፀድቅ እንቅስቃሴ እየተደረገበት ያለው የህግ ረቂቅ ለኢትዮጵያ የሚፈይደው አንዳች ነገር የለም ሲል የማስታወቂያ ሚኒስቴር ገለጸ።ሚኒስቴሩ የመንግስትን አቋም በሚተነትነው ሳምንታዊ ጽሁፉ እንዳስታወቀው ከግል ስሜትና ጥቅም በመነጨ የራስን ፍላጎት በሌሎች ላይ ለመጫን በሚመስል መልኩ በአንዳንድ የአሜሪካ ኮንግሬስ አባላት ግፊት ተዘጋጅቶ ለሴኔቱ ውሳኔ የተላለፈው ይህ ህግ በአንድ ሀገር የውስጥ ጉዳይ ጣልቃ መግባትን ከማመልከቱም በላይ የኢትዮጵያ ነባራዊ ሁኔታን ያላገናዘበና ሚዛናዊነት የጎደለው ነው ብሏል።
ከአሜሪካ ኮንግሬስ አባላት ጎን ተሰልፈው ሕጉ እንዲፀድቅ እየሰሩ ያሉት በሻዕቢያ አስተባባሪነት የሚንቀሳቀሱት ኦነግና ኦብነግ መኖራቸው ለሕጉ መረቀቅ መነሻ ነው የተባለው ምክንያት ምን ያህል የተሳሳተ እንደሆነ እንደሚያመለክትም ገልጿል፡፡ የኢትዮጵያን ሕዝብ ይቅርታ ጠይቀው ከእስር ከተፈቱ በኋላ ወደ አሜሪካ የተጓዙት የቅንጅት አመራር አባላት ለዚህ ሕግ መፅደቅ ደፋ ቀና ሲሉ እንደሚታዩም አመልከቷል፡፡
ዘላቂ እድገትን ለማረጋገጥ የልማት፤ የሰላምና የዴሞክራሲ ሥርዓት ግንባታው በተፋጠነበትና የኢትዮጵያን ህዳሴ በአዲሱ ሚሌኒየም ለማረጋገጥ ሰፊ ርብርብ በተያዘበት በዚህ ወቅት ይህንን ጥረት ለማደናቀፍ በሚያልሙ ኃይሎች የሚሸረብ ሴራ አልፎ አልፎ መከሰቱ አልቀረም ያለው መግለጫው ይህንን የህግ ረቂቅ የሚያንቀሳቅሱ ኃይሎችና ተከታዮቻቸው እጃቸውን ሊሰበስቡ ይገባል ብሏል።
እንደመግለጫው የኢትዮጵያና የአሜሪካ መንግስታት በበርካታ የጋራ ጉዳዮችና ጥቅሞች ላይ በቅርበት እየሰሩ ሲሆን የሁለትዮሽ ግንኙነቱና ትብብሩም ጠንካራ መሰረት ያለው ነው ። በመሆኑም ኤች አር 2003 የህግ ረቂቅ ያካተታቸው መሰረታዊ ሃሳቦች ከዚህ ጠንካራ ግንኙነት ጋር ፈጽሞ ሊጣጣሙ አይችሉም።
ስለሆነም ረቂቅ ህጉ ለኢትዮጵያ ህዝቦች ዴሞክራሲያዊ ግንባታ ብሎም ለሁለቱ ሀገሮች ህዝቦች ግንኙነትና የጋራ ጥቅም የሚፈይድው አንዳችም ጠቀሜታ እንደሌለው ታውቆ በየደራጃው ከወዲሁ ለወገዝ ይገባል ሲል ሚኒስቴሩ አስታውቋል።
ሪ11፡30 ያ12፡25
---END---