አዲስ አበባ, ጥቅምት 15 ቀን 2000 (አዲስ አበባ) - የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋኅዶ ቤተክርስቲያን ቅዱስ ሲኖዶስ ምልዓተ ጉባኤ ሽብርተኝነት ለሰው ዘር ጠንቅ በመሆኑ ሊወገድ ይገባዋል ሲል ጥሪ አስተላለፈ፡፡በብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ጳውሎስ ፓትርያርክ የዓለም አብያተ ክርስቲያናት ፕሬዚዳንትና የዓለም ሃይማኖቶች ለሰላም የክብር ፕሬዚዳንት የተመራው ይኸው ጉባኤ አምስት ቀናት ቆይቶ ዛሬ ከመጠናቀቁ በፊት ጥሪውን ያስተላለፈው ስለዓለም ሰላም ጭምር ባደረገው ውይይት ነው፡፡
ጉባኤው በኤች አይ ቪኤድስ ጥቃት ያለ አሳዳጊና ያለጧሪ የቀሩትንና በበሽታው የተያዙ ወገኖችን ከማፅናናቱ ጎን ለጎን የገንዘብና የቁሳቁስ ድጋፍ መለገስ የሚቻልበትን ሁኔታ በተመለከተ ውሳኔ አሳልፏል፡፡
በተያያዘም በተለያየ ምክንያት ወላጅ አልባ የሆኑ ሕፃናት የሚረዱበትና፣ ጧሪ ያጡ አረጋዊያን የሚጦሩበት ድርጅት ማቋቋም እንደሚያስፈልግ በስፋት የተወያየው የቅዱስ ሲኖዶስ ምልዐተ ጉባዔ በሁሉም አህጉረ ስብከት ድርጅቱ እንዲቋቋምም ወስኗል፡፡
ኢትዮጵያ መካከለኛ ገቢ ካላቸው ሀገራት ጎራ ተቀላቅላ ከድህነት እንድትላቀቅ ለማስቻል መንግሥት ያወጣውን እቅድ የሚደግፍ መሆኑን የገለጸው የቅዱስ ሲኖዶስ ውሳኔ ወጣቱ ትውልድ የስነ እምዕሮ ብቃቱን አሳድጎ ሥራ ፈጣሪ የሚሆንበትን፣ ባለሀብቶችና ኢንቨስተሮች የጀመሩትን የልማት ሥራ በማስፋፋት ለሰመረ ውጤት ይበቁ ዘንድ የሁሉም ሕብረተሰብ ተሳትፎ ወሳኝነት አለው ብሏል፡፡
ፅንስ ማስወረድ በመላው ዓለም እንደ መብት ተቆጥሮ በስፋት እየተከናወነ ነው ያለው የቅዱስ ሲኖዶስ ምልዐተ ጉባዔ ፅንስ ማስወረድ በሃይማኖትና በክርስቲያናዊ ሥነ ምግባር አግባብ ስላልሆነ ቤተክርስቲያናችን ፈፅማ ታወግዘዋለች ብሏል፡፡
በተለያየ ምክንያት በማረሚያ ቤት ይገኙ የነበሩ የሕግ ታራሚዎችን ለማስለቀቅ በተደረገው እንቅስቃሴ ምሕረት ተደርጎላቸው ከህብረተሰቡ ጋር ለመቀላቀል በመብቃታቸው ቅዱስ ሲኖዶስ አድናቆቱን ገልፆ ይህን እድል ለሰጣቸው ለኢትዮጵያ ፌዴራላዊ ዲሞክራሲያዊ ሪፑብሊክ መንግሥት ምስጋናውን አቅርቧል፡፡
የቅዱስ ሲኖዶስ ምልዓተ ጉባዔ የኢትዮጵያ ብሔራዊ ሚሌኒየም ፅህፈት ቤት ባዘጋጀውና ባለፈው ማክሰኞ በተከናወነው ቆም ብለን ድህነትን ለማጥፋት ቃል እንግባ የተሰኘ ፕሮግራም በመላ ሀገሪቱ መከናወኑን አስታውሶ ሁሉም ሕብረተሰብ ድህነትን ታሪክ ለማድረግ መረባረብ ይጠበቅበታል ብሏል፡፡
የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስትያን ቅዱስ ሲኖዶስ ምልዐተ ጉባኤ በተለያዩ አጀንዳዎች ላይ በስፋት ሲወያይ ቆይቶ ባለ አሥራ ሁለት ነጥብ ውሳኔ በማስተላለፍ መጠናቀቁን ከመንበረ ፓትርያርክ ኦዲዮ ቪዠዋል ክፍል የደረሰው ዘገባ ያመለክታል፡፡
ሪ 12፡50 የ1፡02
---END---