አዲሰ አበባ, ጥቅምት 15 ቀን 2000 (አዲስ አበባ) - ካለፈው ጥቅምት 9 ቀን ጀምሮ በብሄራዊ ሙዚየም ''ንግስት ሳባ በትናንትና ጥላ ሥር'' የተባሉ የጥበብ ሥራዎቿን ለሀዝብ ያቀረበችው ስዊትዘርላንዳዊት አርቲስት በኢትዮጵያ ያደረገችው ቆይታ ከልብ ያስደሰታት መሆኑን ገለጸች፡፡ሰዓሊ አልሳባ ጃሚላ ዛሬ በሙዚየሙ አዳራሽ ከጋዜጠኞች ጋር ባደረገችው ቆይታ እንደተናገረችው በኢትዮጵያ የስዕል ሥራዎቿን ለማቅረብ ስትመጣ የሚሊኒየም በዓል እየተከበረ ስለመሆኑ የምታውቀው ነገር አልነበረም፡፡
ይሁንና የበዓሉን አፍሪካዊ ስሜት ካጤነች በኋላ ሃገሪቱ በአፍሪካና በመንግሥታት አንድነት ላይ የምትጫወተው ሚና ጉልህ መሆኑን ለመረዳት መቻሏን ተናግራለች፡፡
በዚህ ወቅት ወደ ኢትዮጵያ በመምጣቷ መደሰቷን ገልጻ በስዕል ሥራዎቿ ልታመላክት የፈለገችውን የመንግሥታትና የሀዝቦች አንድነት ጅማሮ በኢትዮጵያ ውስጥ በገሃድ ማየት በመቻሏም ልዩ ስሜት እንዳደረባት ተናግራለች፡፡
ኢትዮጵያን የምታውቃት በቴሌቪዥንና በሌሎች መገናኛ ብዙሃን እንደነበርና አሁን ግን በገሃድ መጥታ ልታያት በመቻሏ ኩራት የተሰማት መሆኑንም አርቲስቷ ገልጻለች፡፡
አርቲስቷ በ30 የተለያዩ ሃገራት ከ130 በላይ ኤግዚቢሽን በማዘጋጀት ስለንግሥተ ሳባ ያዘጋጀቻቸውን የጥበብ ሥራዎች ለህዝብ ማቅረቧን ተናግራ በዚህም የቀድሞዋን አቢሲኒያና የአሁኗን ኢትዮጵያ ማስተዋወቅ መቻሏን ተናግራለች፡፡
ይሀን የስዕል ሥራ በመያዝ በሚቀጥሉት ጊዜያት የትውልድ ሃገሯ ከተማ የሆነችው ጄኔቫን ጨምሮ የተለያዩ ሃገራትን እንደምታዳርስም አስታውቃለች፡፡
የስዕል ኤግዚቢሽኑ እስከ መጪው ጥቅምት 26 ድረስ ለህዝብ ክፍት ሆኖ ይቆያል፡፡
ሪ11፡10 የ1፡33 ጥ ከ
---END---