አዲስ አበባ, ጥቅምት 15 ቀን 2000 (አዲስ አበባ) - የፍትሕ ሚኒስቴር ያሉበትን የአሰራር፣ የአደረጃጀትና የሰው ኃይል ችግሮች አስወግዶ ተቋማዊ ለውጥ በማምጣት ከመንግሥትና ከሕዝብ የሚጠበቅበትን ኃላፊነት እየተወጣ መሆኑን የፍትሕ ሚኒስትሩ አስታወቁ፡፡
የፍትሕ ሚኒስቴር ጥቅምት 15 ቀን 1900 ዓ.ም የዳኝነት ሚኒስቴር ተብሎ የተቋቋመበትን 100ኛ አመት ምክንያት በማድረግ ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች፣ የተወካዮች ምክር ቤት አባላትና የሚኒስቴር መሥሪያቤቱን ቀደም ሲል በሚኒስትርነት ያገለገሉ በተገኙበት የሚኒስቴሩ ሠራተኞች በአዲሱ ሚሌኒየም ሙሉ አቅማቸውን ተጠቅመው ሕብረተሰቡን ለማገልገል ቃል ገብተዋል፡፡
የሚኒስቴር መሥሪያ ቤቱ አላስፈላጊና ድግግሞሽ የሚታይባቸውን የሥራ ክፍሎች ሰርዞ ወጪን በመቀነስና የተጀመረውን የተቋማዊ ለውጥ ሥራ በሚመራ አዲስ ኃይል በመተካት የሥራ ቅልጥፍና ለማምጣት መቻሉን ሚኒስትሩ አቶ አሰፋ ከሲቶ በዚሁ ጊዜ ተናግረዋል፡፡
ከክልሎች ፍትሕ ቢሮዎች፣ ከምርመራና ከዳኝነት አካላት ጋር የሚያገናኝና የክትትልና ቁጥጥር ሥራ የሚያከናውን ማስተባበሪያ በመቋቋሙ የሥራ ቅልጥፍናና ጥራት ለማምጣት ተችሏል ብለዋል፡፡
ሚኒስትሩ እንዳሉት በፌዴራል የመጀመሪያ ደረጃ እና ከፍተኛ ዓቃቤ ሕግ፣ አዲስ አበባና ድሬዳዋ ምድቦች የወንጀል ምርመራና ድጋፍ ዓቃቤ ሕግ ቡድን በመቋቋሙ ከፖሊስ ጋር በመቀናጀት የወንጀል ምርመራ ሥራን ለመደገፍና ለመከታተል ተችሏል፡፡
ከ100 ሺህ በላይ የነበረው የወንጀል ምርመራ መዝገብ ውዝፍ አሁን ወደ 10 ሺህ የወረደ መሆኑንና የዓቃቤ ሕግ መዝገብ ያለበትን ደረጃ ለማወቅ መቻሉን፣ እንዲሁም ዓቃብያነ ሕግን መገምገም የማይታሰብ የነበረ ሲሆን ተከታታይ ግምገማ በማካሄድ ችግሮችን መለየት፣ መፍትሔዎችን መፈለግና ችግር ፈጣሪዎች በሆኑት ላይ የተለያዩ አስተዳደራዊ እርምጃዎች መውሰድ መቻሉን ገልፀዋል፡፡
ከአመለካከት ችግር የተነሳ ዓቃብያነ ሕግንና ዳኛን ማገናኘት የማይቻል የነበረ ቢሆንም ከጠቅላይ ፍርድ ቤትና ከአቅም ግንባታ ሚኒስቴር ጋር በመተባበር ሁሉኑም ዳኞችና ዓቃብያነ ሕግ በአንድ ላይ በመንግስት ፖሊሲዎች፣ ስትራተጂዎችና በሕገመንግስቱ ላይ የአንድ ወር ሥልጠና ለመስጠት መቻሉን አመልክተዋል፡፡
በፈርድ ቤት ቅጣት የተወሰነባቸው ታራሚዎች አስፈላጊውን መስፈርት አሟልተው ሲገኙ ይቅርታ የሚያገኙበት ሥርአት ተዘርግቶ በርካታ ዜጎች ተጠቃሚ መሆናቸውንና በተለይ በ1998 እና 1999 ዓ.ም ብቻ ከመላ አገሪቱ በትንሹ 30 ሺህ የሚሆኑ ታራሚዎች ይቅርታ አግኝተው ከእስር መለቀቃቸውን ገልጸዋል፡፡
ሪሪ11፡20 የ12፡33
---END---