አዲስ አበባ, ጥቅምት 15 ቀን 2000 (አዲስ አበባ) - በደቡብ ኢትዮጵያ አገር ሲያስሱ በጫካ ውስጥ አድራሻቸውን ያጡት ስድስት ዜጎቻቸው በሕይወት መገኘት የኢትዮጵያ ሕዝብና መንግስት ጥረት ውጤት በመሆኑ እንዳስደሰታቸው የቼክና የስሎቫክ አገራት አምባሳደሮች ገለጹ፡፡በኢትዮጵያ የቼክ ሪፑብሊክ አምባሳደር ዝዴኔክ ዲቢያሽና የስሎቫክ ሪፑብሊክ አምባሳደር ሚላን ሲጋኝ ከአሳሾቹ ጋር በመሆን ለኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት ዛሬ እንደገለጹት ለዜጎቻቸው በሕይወት መገኘት የኢትዮጵያ መንግስትና የአካባቢው ነዋሪ ሕዝብ ከፍተኛ ርብርብ አድርገዋል፡፡
በዳንቺያ ወንዝ ላይ አገር ሲያስሱ አቅጣጫቸው የጠፋባቸው ሰዎችን ከአደጋ ለመታደግ ፈጣን እርምጃ በመውስድ አርዓያነት ያለው ተግባር የኢትዮጵያ መንግሰትና ሕዝብ በመፈጸማቸው ሁለቱም አምባሳደሮች አመስግነዋል፡፡
በተለይ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር የስድስቱ አገር አሳሾች አቅጣጫ መሳትን ከሰማበት ወቅት አንስቶ የአደጋ ሰዎች በሄሊኮፕተር ወደአካባቢው ተደጋጋሚ በረራ በማድረግ ፍለጋው እንዲጠናከር ማድረጉ ትልቅ ተምሳሌት ነው ብለዋል፡፡
አገር አሳሾቹ በበኩላቸው የኦሞ ወንዝ ገባር በሆነውና በውብና ማራኪ አካባቢ ውስጥ በሚገኘው ዳንቺያ ወንዝ የመጀመሪያዎቹ አሳሽ መሆናቸው እንዳስደሰታቸው ገልጸዋል፡፡
ይሁንና የወንዙ አቅጣጫ በጀልባ ዘልቆ ለመዋኘት አስቸጋሪ ሥፍራ ላይ መድረሳቸውን እንዳረጋገጡ ወደኦሞ ወንዝ የሚያደርጉትን ጎዞ ለማቋረጥ መገደዳቸውን ገልጸዋል፡፡
ጥቅጥቅ ባለደን ውስጥ ደግሞ የከፋ አደጋ እንዳይገጥማቸው ወደቼክ ኤምባሲ በሳተላይት ሞባይል የድረሱልን ጥሪ ከሥፍራው ማስተላለፋቸውን ጠቁመዋል፡፡
ይሁን እንጂ የሻማ አካባቢ ነዋሪ ሕዝብ ፈጥኖ በመድረስ ከአስቸጋሪ ስፍራ እንደታደጋቸውና ምግብና ሌሎች ድጋፎችን በማቅረብ ፍቅር በተላበሰ እንክብካቤ ስላስተናገዳቸው አመስገነዋል፡፡
ኢትዮጵያ ውብና ለቱሪስት አመቺ አገር መሆኗን አገር አሳሸሾቹ ገልጸው ሕዝቧም ለእንግዳ መልካም አቀባበል የሚያደርግና ጨዋ መሆኑን መስክረዋል፡፡
በስፍራው የተገኙት የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ከፍተኛ የስራ ኃላፊዎች እንደገለጹት በስድስቱ የቼክና የስሎቫክ ዜጎች በጥቅጥቅ ደን ውስጥ መሰወር ከፍተኛ የኢትዮጵያ መንግስት ባለስልጣናትን በወቅቱ ማሳሰቡን ጠቁመው ሌት ተቀን በተደረገ ጥረት በአጭር ቀናት ውስጥ አድራሻቸው ሊግኝ መቻሉን ተናግረዋል፡፡
አሳኞቹ አካባባቢውን በተመለከተ የተቀረጹትን የቪዲዮ ፊልሞች ለኢትዮጵያ ሕዝብ ገጸበረከት ለመስጠት ፈቃደኛ በመሆናቸው አመስግነዋቸዋል፡፡
ይህ በእንዲህ እንዳለ ሌላ አገር አሳሽ ቡድን ወደስፈራው በቅርቡ እንደሚንቀሳቀስ ከአምባሳደሮቹ መግለጫ ለማወቅ ተችሏል፡፡
---END---