አዲስ አበባ, ጥቅምት 13 ቀን 2000 (አዲስ አበባ) - የኢፌዲሪ ጠቅላይ ሚኒስትር መለስ ዜናዊ ለአራት የፌዴራል መንግሥት የሥራ ኃላፊዎች ሹመት ሰጡ፡፡ የጠቅላይ ሚኒስትር ጽህፈት ቤት ዛሬ ለኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት እንደገለጸው አምባሳደር ዶክተር አዲስዓለም ባሌማ የምርት ገበያ ባለሥልጣን ዋና ዳይሬክተር ፣ አቶ ኃይለሥላሴ ቢሆን የመድኃኒት ፈንድና የመድኃኒት አቅርቦት ኤጀንሲ ዋና ዳይሬክተር ፣ አቶ ሹሙ ተፈራ የሣይንስና ቴክኖሎጂ ኤጀንሲ ምክትል ዳይሬክተር እንዲሁም አቶ ዳዊት ዲቃሶ የመድኃኒት አስተዳደርና ቁጥጥር ባለሥልጣን ምክትል ዳይሬክተር በመሆን ተሹመዋል፡፡
የምርት ገበያ ባለሥልጣን ዋና ዳይሬክተር በመሆን የተሾሙት አምባሳደር ዶክተር አዲስዓለም ባሌማ በተለያዩ የኃላፊነት ቦታዎች ለረጅም ጊዜ መሥራታቸውን ፣ የትግራይ ክልላዊ መንግስት የንግዳና ኢንዱስትሪ ልማት ቢሮ ኃላፊ በመሆን ማገልገላቸውንና ከፍተኛ የሥራ ልምድና የትምህርት ደረጃ ያላቸው መሆናቸውን ጽህፈት ቤቱ ገልጿል ፡፡
በተመሣሣይም ሁኔታ የመድኃኒት ፈንድና የመድኃኒት አቅርቦት ኤጀንሲ ዋና ዳይሬክተርነት ሹመት ያገኙት አቶ ኃይለሥላሴ ቢሆን በተለያዩ መሥሪያ ቤቶች በፋርማሲ ባለሙያነት ፣ በመምሪያ ኃላፊነትና በኢትዮጵያ መድኃኒት አስተዳደርና ቁጥጥር ባለሥልጣን በዋና ዳይሬክተርነት አገልግለዋል፡፡
እንዲሁም ጠቅላይ ሚኒስትር የሣይንስና ቴክኖሎጂ ኤጀንሲ ምክትል ዳይሬክተር አድርገው የሾሟቸው አቶ ሹሙ ተፈራ በተለያዩ የሥራ ኃላፊነት ደረጃዎችና በመምሪያ ኃላፊነት አገልግለዋል፡፡
በተጨማሪም የመድኃኒት አስተዳደርና ቁጥጥር ባለሥልጣን ምክትል ዳይሬክተር በመሆን የተሾሙት አቶ ዳዊት ዲቃሶ በፋርማሲስትነትና በመድኃኒት ምርምር ኃላፊነት ያገለገሉ ባለሙያ መሆናቸውን ጽህፈት ቤቱ አስታውቋል ፡፡
ሪ፡10፡35፣ያ፡10፡45 ኤ2 10፡ 53 ጥ ከ
---END---