ሐረር, ነሐሴ 18 ቀን 1999 (ሀረር) - የሐረሪ ክልል አንደኛ መደበኛ ጉባኤ ለዘንድሮ አመት ስራ ማከናወኛ ከ172 ሚሊዮን ብር በላይ በጀትአጸደቀ ።ጉባኤዉ በተጨማሪ የተለያዩ አዋጆችን በማጽደቅና የካቢኔ አባላት ሹም ሽር በማካሄድ ትናንት ተጠናቋል ፡፡ጉባኤው የክልሉን አስፈጻሚ አካላት እንደገና ለማደራጀትና የብዙሐን መገናኛ ኤጀንሲን ለማቋቋም የወጡ አዋጆችን ጨምሮ የስነ ምግባርና የጸረ ሙስናን ኮሚሽን ማቋቋሚያ አዋጆችን መርምሮ አጽድቆአል፡፡
ለክልሉ ሆስፒታሎች የተመደበው 10 ሚሊዮን ብርም ጥራት ያለው ቀልጣፋ አገልግሎት ለህብረተሰቡ ለመስጠት በቂ ባልመሆኑ የምክር ቤት አባላት በጉዳዩ ላይ በመወያየት ከመጠባበቂያ በጀት ላይ ማሻሻያ እንዲደረግበት ጠቁመዋል፡፡
ጉባኤው የክልሉ የካቢኔ አባልና የህዝብ አደረጃጀት ባህልና ማህበራዊ ቢሮ ሃላፊ አቶ ዘይዳን በክሪ ህዝብና መንግስት የጣለባቸውን ሃላፊነት በብቃት አልተወጡም በሚል ከሃላፊነታቸው እንዲነሱ አድርጐአል፡፡
በምትካቸው አቶ ኢማጅ እንድሪስ የባህልና ህዝብ አደረጃጀት ቢሮ ሃላፊ ሆነው የተሾሙ ሲሆን የትምህርትና አቅም ግንባታ ቢሮ በመለያየታቸው አቶ ረጋሳ ከፍያለው ከክልሉ ምክትል ርእሰ መስተዳድርነታቸው በተጨማሪ የእቅም ግንባታ ቢሮን እንዲመሩ ተሹመዋል፡፡
አቶ ነቢል መሐመድም የትምህርት ቢሮ ሃላፊ እንዲሆኑ በምክር ቤቱ አባላት በሙሉ ድምጽ ተወስኖ ጉባኤው በትናንትናው እለት ተጠናቋል፡፡
---END---